የንግድ ትርኢት የአፈፃፀም መመሪያ

 

የኢፊዲሪ መንግሥት በአሁኑ ወቅት ከምታራምደው የነፃ ገበያ ኢኮኖሚ ፖሊሲ ጋር የማጣጣምና ለህጋዊ የንግድ ሥራ እንቅስቃሴ ምቹ ሁኔታዎችን ለመፍጠር የሚያስችል የንግድ ምዝገባና ፈቃድ አዋጅ ቁጥር 67/89 በማውጣቱና ይህን አዋጅ መሠረት በማድረግ የአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት ምክር ቤት የንግድ ምዝገባና ፈቃድ ደንብ ቁጥር 3/9ዐ አውጥቷል፡፡

 

በዚሁ መሠረት የክልሉን ተጨባጭ ሁኔታ ያገናዘበና የሁሉንም ተጠቃሚነት በአረጋገጠ መልኩ የምርትና የፈጠራ ሥራዎችን ለማስተዋወቅ ፣ የኢንቨስትመንት ዕድሎችን የሚዳስሱ አማራጮችን ለመፍጠርና የክልሉን የኢንዱስትሪና የእርሻ ምርታማነትን ለማሻሻል፣ የቴክኖሎጅ ሽግግርን የባህልና የሀሣብ ልውውጦችን ለማዳበር፣ ገቢያን ለመሞከርና በምርት ላይ ያተኮረ የሻጭና የገዥ የአገልግሎት አሰጣጥ ግንኙነት አድማስንና ንግድን ለማስፋፋት የሚያስችል የንግድ ትርኢት የአፈፃፀም መመሪያ ማውጣት በማስፈለጉ፣

 

የአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት ንግድና ኢንዱስትሪ ቢሮ በኢፊዲሪ የንግድ ምዝገባና ፈቃድ አዋጅ ቁጥር 67/89 አንቀጽ 39 መሠረት ይህን መመሪያ አውጥቷል፡፡

 

ክፍል አንድ

ጠቅላላ

አንቀጽ 1 አጭር ርዕስ

ይህ መመሪያ “ በአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሰት የንግድ ትርኢት ለማዘጋጀት የወጣ የአፈፃፀም መመሪያ” መመሪያ ቁጥር ዐ2/99 ተብሎ ሊጠቀስ ይችላል፡፡

 

አንቀጽ 2 ትርጓሜ

የቃሉ አግባብ ሌላ ትርጉም የሚያሰጠው ካልሆነ በስተቀር በዚህ መመሪያ ውስጥ

1.     “ቢሮ” ማለት በአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት የንግድና ኢንዱስትሪ ቢሮ ነው፡፡

2.     ”የንግድ ትርኢት” ማለት በዚህ የአፈፃፀም መመሪያ መሠረት ንግድን የማስፋፋት ዓላማ ያለው ለተወሰኑ ቀኖች ብቻ የንግድ ዕቃዎችን መሣሪያዎችን፣ የኢንዱስትሪና የእርሻ ውጤቶችን፣ የፈጠራ ውጤቶችንና ልዩ ልዩ አገልግሎቶችን ወዘተ ለህዝብ እይታ ወይም ለሽያጭ በማቅረብ የሚካሄድ ተግባር ነው፡፡

3.     “ ነጋዴ” የሚለው ቃል በአዋጅ ቁጥር 67/89 አንቀጽ 2 ንዑስ አንቀጽ 2 የተሰጠውን ትርጉም ይይዛል፡፡

4.     “ ሰው” ማለት ማንኛውም የተፈጠሮ ሰው ወይም በህግ የሰውነት መብት የተሰጠው ድርጅት ነው

5.     “ አዘጋጅ” ማለት የንግድ ትርኢት ለማዘጋጀት በዚህ መመሪያ መሠረት ፈቃድ የሰጠው ሰው ወይም ድርጅት ነው፡፡

6.     “ማመልከቻ” ማለት በዚህ መመሪያ መሠረት የንግድ ትርኢትን ለማዘጋጀት የሚቀርብ የጽሁፍ ጥያቄ ነው፡፡

7.     “ ፈቃድ” ማለት በዚህ መመሪያ መሠረት የንግድ ትርኢት ለማካሄድ በቢሮው ለአዘጋጁ የሚሰጥ የፁሁፍ ማረጋገጫ ነው፡፡

8.     “ ውል” ማለት የንግድ ትርኢት ለማካሄድ ፈቃድ የተሰጠው አዘጋጅ ስለ ንግድ ትርኢቱ አጠቃቀም ሁኔታ የተዘረዘሩ መብቶችና ግዴታዎችን ለማክበር የተፈረመ የስምምነት ሰነድ ነው፡፡

 

አንቀጽ 3 የአፈፃፀም ወሰን

ይህ የአፈፃፀም መመሪያ በአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት ውስጥ የንግድ ትርኢት በሚያዘጋጅ ሰው/ድርጅት ላይ ተፈፃሚ ይሆናል፡፡

 

ክፍል ሁለት

አንቀጽ 4 ፈቃድ ሲሰጥ ሊሟሉ የሚገባቸው መመዘኛዎች / መስፈርቶች/

  1. ፈቃድ ጠያቂው የፀና የንግድ ሥራ ፈቃድ ሊኖረው ይገባል ሆኖም ለአንድ ለተለየ አላማ የንግድ ትርኢት የሚያዘጋጅ መንግስታዊ/ ህዝባዊ የሆኑ ድርጅቶችንና የሙያ ማህበራትን አይመለከትም፡፡
  2. ፈቃድ ጠያቂው የንግድ ትርኢት በማዘጋጀት ተሞክሮ/ ልምድና የመልካም ሥራ አፈፃፀም ማስረጃ ያለው ቢሆን ይመረጣል፡፡
  3. አዘጋጁ በዚህ የአፈፃፀም መመሪያ መሠረት ግዴታዎች መፈፀም አለበት፡፡
  4. የክልሉን እድገት ሊያፋጥኑና ሊያበረታቱ የሚችሉ የንግድ ትርኢቶችን ለሚያዘጋጁ ቅድሚያ ይሰጣል፡፡
  5. ከላይ በፊደል ተራ ቁጥር “ ለ” እና “ መ” የተጠቀሱት እንደተጠበቁ ሁኖ የማመልከቻ ቅድሚያ ግምት ውስጥ ይገባል፡፡
  6. የንግድ ትርኢት በተናጥል ወይም በጋራ ሊከናወን ይችላል፡፡  ሆኖም ፈቃድ የሚሰጠው በአንድ ሰው ወይም ድርጅት ስም ብቻ ሲሆን በጋራ ለማዘጋጀት የሚፈልጉ ሰዎች ወይም ድርጅቶች ከሆኑ ስምምነታቸውን ከማመልከቻቸው ጋር አያይዘው ካቀረቡ እንደ ስምምነታቸው ፈቃዱ የሚሰጣቸው ይሆናል፡፡

 

 

አንቀጽ 5 የአዘጋጁ ግዴታዎች

  1. በንግድ ትርኢቱ እንዲሣተፉ የሚጋበዙ ነጋዴዎች፣ ድርጅቶች ካምፖኒዎች ወዘተ የፀና የን/ሥ/ፈቃድ ያላቸው መሆኑን ማረጋገጥ አለበት፡፡
  2. የንግድ ትርኢት ለማዘጋጀት የሚቀርብ ጥያቄ ትርኢቱ ይከናወናል ተብሎ ከታቀደበት ጊዜ 3 ወር አስቀድሞ መቅረብ ይኖርበታል፡፡
  3. የንግድ ትርኢቱ ክፍት ሁኖ የሚቆይበት ጊዜ ከ12 ቀን መብለጥ የለበትም፡፡ ሆኖም በአዘጋጅ ጥያቄ ሲቀርብ እንደአስፈላጊነቱ ለ3 ተጨማሪ ቀናት ሊራዘም ይችላል፡፡
  4. በንግድ ትርኢቱ የሚቀርቡ ዕቃወች ሕጋዊ ቀረጥ የተከፈለባቸው፣ በህብረተሰቡ ላይ የጤና ፣ የባህል ወይም ሌላ ችግር የማያስከትሉና የምርቶች ጥራት ደረጃቸውን የጠበቁ እንዲሆኑ ይጥራል፡፡ ጉዳዩን ከማረጋገጥ አኳያ የሚመለከታቸው የመንግስት መስሪያ ቤቶች ቁጥጥር ሊያደርጉ ይችላሉ፡፡
  5. አዘጋጅ የንግድ ትርኢቱን አዘጋጅቶ ከፈፀመ በኋላ በታሰበለት አላማ መሠረት መካሄዱን፣ የተሣታፊ ድርጅቶችን ብዛት፣ የተለያዩ አካላት የተደረገን ድጋፍ፣ ያጋጠሙ ችግሮች ተለይተው አጭር ሪፖርት ትርኢቱ በተካሄደበት ለሚገኝ ን/ኢ/ቅ/ጽ/ቤት የማቅረብ ግዴታ አለበት፡፡
  6. አዘጋጅ በተፈቀደለት ጊዜ ትርኢቱን ማካሄድ ካልቻለ ወይም በፈቃዱ መጠቀም አለመቻሉን ሲረዳ ከበቂ ማስረጃ ጋር ትርኢቱ ይከፈታል ተብሎ ከታሰበበት ጊዜ አንድ ወር አስቀድሞ ለቢሮው የማሣወቅ ግደታ አለበት፡፡ ትርኢቱ ስለመቋረጡ ወይም መቅረቱ ቅስቀሳ ባደረገበት የማስታወቂያ ዘዴ ማሳወቅ ይኖርበታል፡፡
  7. የንግድ ትርኢቱ የሚዘጋጅበት ቦታ ለተገልጋዩ አመች የሆነ መጠለያ፣ በጤና ላይ ችግር የማያስከትል፣ የሌሎች ነጋዴዎችን ንግድ ልውውጥ የማያቋርጥና የአካባቢ ኗሪዎች ደህንነት የማያውክ መሆኑን ማረጋገጥ አለበት፡፡
  8. አዘጋጁ በዚህ አፈፃፀም መመሪያ ውስጥ የተዘረዘሩትን፣ ሌሎች ቢሮው የሚጠይቃቸውንና የንግድ ትርኢቱን በተፈቀደለት አላማ መሠረት ተግባራዊ የማድረግ ግደታ አለበት፡፡

 

አንቀጽ 6 የቢሮው ተግባርና ኃላፊነት

  1. በክልሉ ለሚዘጋጅ የንግድ ትርኢቶች ፈቃድ ይሰጣል
  2. የንግድ ትርኢት ለማዘጋጀት ጥያቄ ሲቀርብ በዚህ መመሪያ አንቀጽ 4 ለተዘረዘሩት መመዘኛዎች ተሟልተው ከተገኙ በ5 የሥራ ቀናት ውስጥ ፈቃድ ይሰጣል፡፡
  3. በአዘጋጁ ጥያቄ ሲቀርብ ወይም በሌላ ሁኔታ የንግድ ትርኢቱ የመክፈቻ ጊዜ እንዲራዘም አስፈላጊ ሁኖ ሲገኝ ሁኔታውን በመመርመር ሊፈቅድ/ሊወስን ይችላል፡፡ ሆኖ የመክፈቻ ጊዜን ለማራዘም የሚቀርብ ጥያቄ ትርኢቱን ለመክፈት ታስቦ ከነበረው ጊዜ ከ15 ቀን ቀደም ብሎ መቅረብ አለበት፡፡
  4. የንግድ ትርኢቱ በመመሪያው መሠረት እየተከናወነ ስለመሆኑና በህብረተሰቡና በንብረት ላይ አደጋ እንዳይደርስ ለመቆጣጠር የራሱን ስልት ይቀይሳል፡፡
  5. ለትርኢቱ መሣካት የበኩሉን ድጋፍና ትብብር ያደርጋል
  6. የንግድ ትርኢት ፈቃድ ሲሰጥ በወቅቱ ለክልሉ ገቢዎች ባለስልጣን ያሣውቃል
  7. የንግድ ትርኢት አዘጋጁ ከመመሪያ ውጭ ለሚፈጽማቸው ማናቸውም ሁኔታዎች በአንቀጽ 7 የተዘረዘሪሩትን እርምጃዎች ተግባራዊ ያደርጋል፡፡
  8. የንግድ ትርኢቱ የሚካሄደው በግለሰቦች ወይም በድርጅቶች መካከል በተደረሰ ስምምነት መሠረት በጋራ ሆኖ በመካከላቸው አለመግባባት ቢፈጠር አስፈላጊውን እርምጃ በመውሰድ የንግድ ትርኢቱ የሚቀጥለበትን ሁኔታ ያመቻቻል፡፡
  9. እንደ አስፈላጊነቱ በክልሉ ውስጥ የሚካሄዱ የንግድ ትርኢቶች አንድ ተጓዥ የሚሆንበትን መንገድ ሊያመቻች ይችላል፡፡

 

አንቀጽ 7 በቢሮው ስለሚወሰዱ አስተዳደራዊ እርምጃዎች

 

አዘጋጁ በመመሪያው ከተመለከተው ውጭ ትርኢቱን እያካሄደ መሆኑ ሲረጋገጥ ቢሮው ድርጊቱን በጥሞና በመመርመር የሚከተሉትን እርምጃዎች ይወስዳል፡፡

  1. የንግድ ትርኢቱ እንዳይካሄድ / በመካሄድ ላይ ያለው ትርኢትም ቢሆን እንዲቋረጥ፣ የማድረግ
  2. በክልሉ ውስጥ ሌላ የንግድ ትርኢት በአዘጋጁ እንዳይካሄድ ላልተወሰነ ጊዜ የማገድ
  3. እንደአስፈላጊነቱ ሌሎች ተመጣጣኝ እርምጃዎችን የመውሰድ ፣ስልጣን አለው፡፡

 

አንቀጽ 8 ለትርኢቱ ስለሚቀርቡ ዕቃዎች

 

በዚህ መመሪያ መሠረት ከውጭ አገር ለንግድ ትርኢት የሚቀርቡ እቃዎች ለሽያጭ ሣይሆን ለትይንት የሚውሉ ከሆነ መጠናቸው በየአይነቱ

v        ኤሌክትሮኒክስ እቃዎች እስከ----------------------3

v        ሌሎች በቁጥር የሚለኩ እስከ --------------------5

v        በፖኬት እስከ ---------------------------------------5

v        በኪሎ ግራም /እሽግ/ እስከ ------------------------2 በኩንታል

v        በሊትር እስከ ---------------------------------------- 2ዐዐ ሊትር

 

ሆኖ ለሽያጭ የሚቀርብ ከሆነ ግን መደበኛውን የውጭ ንግድን በተከተለ መልኩ ተፈፃሚ ይሆናል፡፡

 

 

አንቀጽ 9 ስለንግድ ትርኢት ፈቃድ ክፍያ

 

በዚህም መመሪያ መሠረት ለሚሰጥ የንግድ ትርኢት ፈቃድ ብር 2ዐዐ /ሁለት መቶ / ለቢሮው ይከፈላል፡፡

 

ክፍል ሶስት

ልዩ ልዩ ሁኔታዎች

አንቀጽ 1ዐ ፈቃድ ለመጠየቅ የሚቀርብ ማመልከቻ

 

የንግድ ትርኢት ለማዘጋጀት የሚቀርብ ማመልከቻ

  1. አድራሻው ለቢሮው መሆን አለበት
  2. የንግድ ትርኢቱን አላማ ያካተተ መሆን አለበት
  3. የንግድ ትርኢቱ የሚካሄድበትን ቦታና ጊዜ መለየት ይኖርበታል
  4. ፈቃድ ጠያቂው ወይም ጠያቄዎች/ በሕጋዊ ወኪሉ ተፈርሞ መቅረብ ይኖርበታል፡፡
  5. የአዘጋጁን ስምና ሙሉ አድራሻ መግለጽ አለበት፣
  6. ፈቃድ ጠያቂው  የፀና የንግድ ሥራ ፈቃድን ፎቶ ኮፒ አያይዞ ማቅረብ አለበት፡፡

 

አንቀጽ 11 የንግድ ትርኢት ስለማቋረጥ

የተከፈተው የንግድ ትርኢት ሊቋረጥ የሚችለው በቢሮው ውሣኔ ብቻ ይሆናል፡፡

 

አንቀጽ 12 ስለማሻሻል

 

ይህ መመሪያ እንደአስፈላጊነቱ በቢሮው ሊሻሻል ይችላል፡፡

 

አንቀጽ 13 መመሪያው ስለሚፀናበት ጊዜ

 

ይህ የአፈፃፀም መመሪያ ከ --------------------ጀምሮ የፀና ይሆኖል፡፡